Wednesday, March 13, 2013

የስነ - ህዝብ ለውጦች

በአለም ላይ በስነ-ህዝብ በኩል መሰረታዊ ለውጦች በመታየት ላይ ይገኛሉ ። በአንድ በኩል የምእራባውያን ህዝብ በእድሜ መግፋትና ማርጀት ብሎም ፣ በእድሜ ለገፉት የሚደረግ የህክምና እና ፣ የጡረታ ወጪዎች ሲሆኑ በሌላ በኩል ደግሞ የወጣት ቁጥር መመናመን በተለይም በአውሮፓና በጃፓን ይህ በስፋት ተስተውሏል ። አውሮፓውያን እያነሰ የመጣውን ህዝባቸውን ቁጥር ከፍ ለማድረግ የሰራተኛ ሀይል ለማግኘት የግድ ከጎረቤት አገራት የውጭ አገር ዜጎችን ወዳገራቸው ማስገባት ግዴታቸው ነው ፣ በተለይም በህክምናው ዘርፍ እንደ ነርስ የመሳሰሉት ሙያዎች በርካታ ወጣቶችን የሚጠይቁ ናቸው ።


በሌላ በኩል ደግሞ የእስያ ሀገራት እንደ ቻይናና ህንድ ያሉት ደግሞ የስነ - ህዝብ ስብጥር «ዲሞግራፊ» እና የፆታ ቁጥር መዛባት ተስተውሏል ። ቻይና ለአመታት በተከተለችው አንድ ልጅ የመውለድ «One Child Policy» የስነ-ህዝብ ፖሊሲ ምክንያት ወላጆች ለሚወልዱት ልጅ አንድ ልጅ ወንድ ልጆችን በመምረጣቸው ምክንያት የወንዶቹ ቁጥር እየጨመረ ሲሄድ በአንፃሩ ደግሞ የሴቶች ቁጥር መመናመንንና ፣ ወንዶች ለትዳር በሚደርሱበት ወቅት በቂ የሴቶች ቁጥር የማይኖርበት ሁኔታ ሲፈጠር ፣ ቻይናውያን እንደ ፊሊፒንስ ካሉ የጎረቤት አገራት የትዳር አጋር እስከ መፈለግ ደረጃ ደርሰዋል ።


በህንድና በቻይና የፅንሱን ፆታ በመለየት ሴት ከሆነች የማስወረድ ድርጊት ስለሚፈፀም በአስር እና ሀያ አመታት ውስጥ በእነኚህ ሀገራት የስነ-ህዝብ ስብጥሩ እንዲዛባ ምክንያት ሆኗል ። በህንድም እንዲሁ በሴቶች ላይ ለሚደርሱ ፆታዊ ጥቃቶች አንዱ መነሾ ተደርጎ የተወሰደው ነገር ይሄው የሴቶች ቁጥር ከወንዶቹ ጋር ተመጣጣኝ አለመሆን ነው ።

በአንፃሩ አህጉረ አፍሪካ ወጣት የሆነ እና ብዛት ያለው የሰራተኛ ሀይል ያለው ሲሆን ፣ የበርካታ ሀገራት ህዝብ ብዛትም እየጨመረ እንደሚሄድ ይገመታል ። ይህም ለአህጉሪቱ እድልን እና ፈተናዎችን ይዞ እንደሚመጣም ይጠበቃል ። እድሎቹ ሰፊ ገበያ ፣ በቂ ሰራተኛ ሀይል ሲሆኑ ፣ ፈተናዎቹ ደግሞ ባልተሟላ መሰረተ ልማት ላይ የተመሰረተ መሆኑ ለአገራቱ ኢኮኖሚ ፈተና ሊጋርጥ ይችላል ።

No comments:

Post a Comment