Wednesday, December 5, 2012

የምጣኔ ሀብት አስተዳደር




አሁን የምንኖርባት አለማችን በየቀኑ እየተለወጠችና እየጠበበች በመምጣት ላይ ትገኛለች ።በብዙ ዘርፎች ከፖለቲካና ከቴክኖሎጂ ለውጥ ጀምሮ ቴክኖሎጂ እያደገና የንግድ ልውውጦች እየተስፋፉ በሄዱ ቁጥር የእርስ በእርስ ግንኙነቶችም እንደዚያው እያደጉ እና እየተለወጡ ይሄዳሉ ። ይሄ ብቻ ሳይሆን አለማችን ይበልጥ እማትጨበጥ ፍሉድ አንዳንድ ጊዜም ይበልጥ ውስብስብና አደገኛ እየሆነች በመሄድ ላይ ትገኛለች ። ለዚህ ዋናው ምክንያቱ አለማችን ከዚህ በፊት ታይቶ በማይታወቅ ሁኔታ እርስ በእርስ የተሳሰረች በመሆኗና አንዱ ባንዱ ላይ ያለው ጥገኝነት እየጨመረ በመሄዱ ነው ። ለዚህ የህዝቦችና የሀገሮች ትስስር ከፍተኛውን አስተዋፅኦ ያደረገው ደግሞ ምጣኔ - ሀብታዊ ትስስሮሽ ሲሆን ፣ ከመቼውም ጊዜ ይበልጥ የምጣኔ ሀብት እውቀትና መረጃ አስፈላጊነት ጎልቶ ይታያል ።

ለዚህ አይነተኛ ምሳሌ የሚሆነው በአንዱ ሀገር ኢኮኖሚ ችግር ቢከሰት ወዲያውኑ ወደ ተቀረው የአለማችን ክፍል ከዚህ ቀደም በታሪክ ታይቶ በማይታወቅ ሁኔታ ይስፋፋል። በአሁኑ ሰአት አንድ ሀገር ምጣኔ - ሀብት ከብዙ ነገሮች ጋር የተሳሰረ ነው ። ለምሳሌ የሀገራችንን ወንዞችን ብንወስድ አሁን በፊት ያለስራ ሲውሉ የቆዩ ቢሆንም አሁን ግን ከሀገሪቱ የምጣኔ ሀብትም ሆነ የፖለቲካ ጉዞ ጋር ቀጥታ ትስስር ያላቸው ጭምር ናቸው ። ወጣቶችን ብንወስድ በአሁኑ ወቅት በአንድ ሀገር ያለ የወጣቶች ሁኔታ - ያደገም ይሁን ያላደገ ሀገር - የዛን ሀገር የምጣኔ - ሀብትና የፖለቲካ እጣ - ፋንታ እሚወስበንበት ደረጃ ላይ ደርሷል ። የብዙ ነገሮች ትስስር ከዚህ በፊት ይታሰብ ከነበረው የበለጠ ነው ።


በአሁኑ ሰአት በአለማችን ላይ ምጣኔ - ሀብት አስፈላጊነት ከማንኛውም ጊዜ በበለጠ አስፈላጊነቱ እየጨመረ የመጣበት ዘመን ላይ ደርሰናል ። በአለም ላይ ከዚህ በፊት በታሪክ ታይተው የማይታወቁ የምጣኔ - ሀብት ችግሮች በመታየት ላይ ሲሆኑ ፣ ለመፍትሄዎቻቸውም በመንግስታት ብቻ የሚፈቱ እንዳልሆኑ ከችግሮቹ ጥልቅነት የተነሳ መገነት ይቻላል ።   


በአሁኑ ሰአት አለማችን የመላው የሰው ዘር እየሆነች በመሄድ ላይ ስትሆን ፣አንደ ሰው የፈለገ ሀገር ፣ በሚፈልገው የአለም አካባቢ ሄዶ መኖር የሚችል ሲሆን ፣ ታዋቂው ሊባኖሳዊ ገጣሚ ካህሊል ጂብራን ሁሉም ማንም ሰው የትም ቢሆን አገሩ ነው የሚል ሀሳብን ያቀርባል ። በአንድ ሀገር ውስጥም ከተለያዩ የአለማችን ክፍሎች የተውጣጡ ሰዎች በተለያዩ የአለማችን ሀገራት ከአሁን ቀደም ታይቶ በማይታወቅ ሁኔታ እንደሚኖሩ ይጠበቃል ።   


ከዚህ በኋላ በአለም ላይ በየትኛውም ሀገር የውስጥ ጉዳይ የሚወሰነው በዋናነት በኢኮኖሚ ጉዳይ ይሆናል ። የብዙ ሀገራት መሪዎችም ስለ ኢኮኖሚው እንቅስቃሴ የተወሰነ ሙያዊ ግንዛቤ እንዲኖራቸው ሲጠበቅ ፤ ሀገራት ከኢኮኖሚ ውጪ ሌላ እንደ ቀድሞው የድንበር ውዝግብ ወይም ጦርነት ጉዳይ በብዙው የአለማችን ክፍል የለም - ጥቂት ከሆኑ የአለማችን ክፍሎች በስተቀር በእነሱም አካባቢ ጉዳዮች በእንጥልጥልና ባሉበት ቆመው ነው ያሉት እንጂ የፖለቲካና የአስተሳሰብ ልዩነቶች እንዳሉ ሆነው ፤ በሀገራት መሀከል እንደ ቀድሞው ጊዜ የተጧጧፈ ጦርነት እሚካሄድበት ሁኔታ የለም ።


የሀገር መሪዎችም ዋናው ከሚጣልባቸው ግዳጆች አንዱና ዋናው ሀገራዊ ማእዱን ማስፋት ሲሆን ሀገራዊ ማእዱ ከሰፋ ለብዙ ዜጎች የተሻለ የስራ እድል ፣ የገቢ እድል ፣ ለመኖሪያ አስፈላጊና ምቹ የሆኑ ነገሮችን ማመቻቸት ይቻላል ። ነገር ግን ሀገራዊ ማእዱ አነስተኛ ከሆነ ግን ለብዙሀኑ ዜጎች የሚዳረስ ነገር ስለማይኖር እርስ በእርስ መበጣበጥና ሙስና የመሳሰሉት የፍትህ መጓደሎች ይከሰታሉ ።   


ቀደም ባለው በአውሮፓ አስከ ህዳሴው (Renaissance) ዘመን ብንወሰድ አንድ መሪ ማወቅ አለበት ተብሎ የሚታሰበው የጦርነትን ጥበብን (The Art of War) ማወቅ የነበረበት ሲሆን በዛን ግዜ በነበረው የአለማችን ሁኔታ የብዙ ሀገሮች እንዲሁም መሪዎች እና የነገስታት ህልውና እሚወሰነው በጦርነት በሚያመጡት ድልና ሽንፈታቸው የነበረ በመሆኑ ነው ። ነጋሲዎችና ልጆቻቸውም በቤተመንግስት ውስጥ በአብዛኛው እሚሰጣቸው ስልጠናም ይኀው የጦርነት ጥበብ እና ስልት ነው ። በርካታ የዘመኑ ምሁራንም በዚሁ በጦርነት ጥበብ ጉዳይ ላይ በርካታ ድርሳኖችን አበርክተዋል ። ለዚህም አይነተኛ ምሳሌዎች ቻይናዊው ሱን ዙ ፣ ቮን ክላሽዊትዝ እና በጦርነት ጥበብ ላይ አሁንም ድረስ እሚሰራባቸውን በርካታ ሀሳቦችን አመንጭተዋል ። 

አሁንም ቢሆን ባለችው አለማችን ከምጣኔ-ሀብት በፊት የሚቀድመው ደህንነት መሆኑ ግልፅ ነው ። አንደ አገር ራሱን መከላከል ከቻለ ብቻ ነው በኢኮኖሚ ሊያድግ የሚችለው ፤ የራሱን ደህንነት ማስጠበቅ ያልቻለ ሐገር ስለኢኮኖሚ እድገት ሊያወራ አይችልም ። እነ አሪስቶትልን የመሳሰሉ የጥንት ግሪካውያን ፍለፍልስፍናን፣ ህግን ከምጣኔ-ሀብት ያስቀድሙ ነበረ ። ምጣኔ-ሀብትን በኤቲክስ የትምህርት ዘርፍ ውስጥ ከተውት የነበረ ሲሆን ይህም በነጋዴ በስነ-ምግባር የታነፀ መሆን አለበት ከሚል እሳቤ በመነሳት ነው ። አብዛኛውን የዘመናዊውን አለም የንግድን ስርአትን መሰረት የጣሉት የጥንት አይሂደሁዳውያን ናቸው ፡። ንግድ እንደ ዝቅተኛ ስራ በሚታይበት ዘመን ሐገር አልባ የነበሩት አይሁዳውያን የአክስዮን ገበያን ፣ የአክስዮን ደረሰኝ ፣ ዘመናዊ ባንክን የመሳለሰሉትን የንግድ አሰራሮችን የፈጠሩት እነሱው ናቸው ።


በሀገራችንም ብንወስድ አመራርን የሚያስረዳው መፅሀፍ ፍተሐ - ነገስት ሲሆን ዝርዝር የአመራር መንገዶችን አለማዊም መንፈሳዊም መንገዶችን የሚጠቁም ሲሆን ፤ የጥንት አባቶቻችን ስለ አስተዳደር ምን ያህል ትኩረትን ይሰጡት እንደነበረ የሚያሳይ ነው ። ነገር ግን ፍትሐ - ነገስት ለብዙሀኑ ህብረተሰብ እንደ አሁኑ ዘመናዊ ትምህርት የሚሰጥ ሳይሆን የነገስታት ልጆች ብቻ ራቅ ብለው የሚማሩት ነበር ይባላል 1።  


ቀደም ያሉት የአውሮፓ ፀሀፍትም መሪዎች እንደ ሰውም እንደ አውሬም መሆን አለበት ሲሉ ይህንን ከግምት ውስጥ በማስገባት ነው ። ይህም በዘመኑ የነበረውን የእርስ በእርስ ጦርነትና መተላለቅን  ፣ ከኛው ዘመነ መሳፍንት ጋር የሚመሳስሰል የእርስ በእርስ የማያቋርጥ ግጭቶችን ከግምት ውስጥ በማስገባት ነው እና ለዛም ነገስታትና መሪዎች ራሳቻቸውን ከጥቃት መከላከል አለባቸው ከሚል እሳቤ በመነሳት ነው  ።


በአሁኑ በአለም በየትኛውም ሀገራት ያሉ የአለም ህዝቦች ዋነኛው ጥያቄያቸው ምጣኔ - ሀብት ሲሆን ፤ እንደ ቀድሞው ሌላ ሀገር ላይ ጦር ለማዝመት ፣ ወይም የሌላን ሀገር ግዛት ለመያዝ የሚታሰብበት ዘመን አብቅቷል ማለት ይቻላል ። አለም እርስ በእርስ የተሳሰረች መሆኗንም በመረዳት በአንዱ ሀገር የተፈጠረ ችግር ለሌላውም የሚተርፍ መሆኑ በአለም ህዝብ ዘንድ ግንዛቤ ተይዟል ። ስለዚህ በአንደኛው መጎዳት ሌላው የሚያተርፍበት ሁኔታ በአሁኗ አለማችን ተቀባይነቱ እየቀነሰ መቷል ። የሀገራት መሪዎችም እንዲሁ በአንዱ ሀገር የሚፈጠር የምጣኔ - ሀብት ችግር ወደ እነሱም ሊመጣ እንደሚችልና ለዛም ዝግጅት ማድረግንና ሊተላለፉ የሚችሉ ችግሮችን መረዳትና ለመቋቋም የሚያስችል እርምጃን መውሰድ የሚያስችል አቅምን መፍጠር ይኖርባቸዋል ።


አሁን ባለችው ግን አለማችን ሀገሮች ከውጭ እስካልተወረሩ ድረስ ፣ ጥቅማቸውን በጦርነት የሚያስከብሩበት ጊዜ አይደለም ። ግዙፍ ወታደራዊ አቅም ያላቸው ሀያላን ሀገራትም ጭምር ይሄን ቢያደርጉ የሚያስከትለውን አንድምታ በአግባቡ ይረዳሉ ። ይህ ብቻ ሳይሆን እርስ በእርሷ በብዙ ነገር ይበልጥ እየተሳሰረች በሄደችው አለማችን ወታደራዊ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ፤ እውቀት ከፍተኛ ደረጃ ላይ በደረሰበት በዚህ ወቅት በሀገራት መሀከል ጦርነቶች ቢካሄዱ ሊያደርስ የሚችለውን ጉዳትና እና ውድመት መገመት አያስቸግርም ።


ያ ብቻ ሳይሆን የምእራብ አገራት በተለይም በእዳ ውስጥ የተዘፈቁት ሀገራት እንደ ቀድሞው በጀት መድበው መደበኛ ጦርነትን ለማድረግ የሚያስችል ፣ እንዲሁም ግዙፍ ወታደራዊ አቅምን የሚያንቀሳቅስ አቅም የሌላቸው ሲሆን በአብዛኛው በአለም ዙሪያም ለዚህ አይነት ጦርነቶች የህዝብ ድጋፍ የለም ማለት ይቻላል ። 

ከዚያ ወዲህ ባለው ጊዜያቶች ግን የጦርነት አመራር፣ የወታደራዊ ስልትና ስትራቴጂ እውቀት ወዳላቸው ጄኔራሎችና የጦር መሪዎች ሲተላለፍ የፖለቲካ አመራሩ ግን ወደ ፖለቲከኞች ተዛውሯል ። አንድ ሀገር ወረራ ወይም ጥቃት ቢያጋጥመው ከፖለቲከኞች የሚጠበቀው አመራር የመስጠት ሲሆን ወደ ተግባር እሚያሸጋግሩት ግን የጦር አዛዦች ናቸው ። የአሁኑ የፖለቲካ መሪው እንደ ቀድሞ በሜዳ ላይ እሚደረጉ የጦርነት ስልቶችን ማወቅ አይጠበቅበትም ።


ነገር ግን ዶላር ከአለም ምጣኔ - ሀብት መድረክ ላይ ቀስ በቀስ እየወረደ ሊሄድ ይችላል ። ለምሳሌ ቻይናና ጃፓን በአመት ወደ 350 ቢሊየን ዶላር የሚገመተውን ንግዳቸውን ቀድሞ በዶላር አማካይነት ያካሂዱ የነበረ ቢሆንም በ2011 ግን ንግዳቸውን በቀጥታ በየራሳቸው ገንዘብ ለማካሄድ ወስነዋል ። ዶላርን ገዝተው ያካሂዱ በነበረው ንግድ የውጭ ምንዛሬውን ለመግዛት ገንዘብ ያስወጣቸው የነበረ ሲሆን ፣ አሜሪካ ገንዘቧ የአለም ኢኮኖሚ መገበያያ መሆኑ ለራሷ ለአሜሪካ ትልቅ ጥቅም እንዳለው ይታወቃል ። ነገር ግን ሀገሮች በእንዲህ አይነት መንገድ በየራሳቸው ገንዘብ ንግዳቸውን የሚያካሂዱ ከሆነ የዶላርን ተፈላጊነት እና ዋጋውን እያወረደው እንደሚሄድ ግልፅ ነው ።


ምሳሌ ብንወስድ ፣ ስታር ባክስ በአንድ ፓውንድ 3 ዶላር ገዝቶ በ13 ዶላር ነው የሚሸጠው በጥሬው የገዛውን ቡና በዚህን ያክል ዋጋ ነው ለገበያ የሚያቀርበው ። ምንም እሴረት ያልተጨመረበትን ቡና በጥሬው ከሀገራችን ገዝቶ የዚህን ያክል ያተርፍበታል ።



እ.ኤ.አ ከ2008 የአለም የገንዘብ ቀውስ ወዲህ አውሮፓውያንን ብንወስድ ለምሳሌ እ.ኤአ. በ2011 ግሪክና ጣሊያን በእዳ ውስጥ በተዘፈቁበት ወቅት  በህዝብ ያልተመረጡ ነገር ግን ምጣኔ - ሀብት  ባለሙያ ሆኑ ባለሙያዎች (Technocrats) ወደ ስልጣን የመጡበት ሁኔታ ነበረ ። ቀውሱ በጣም አሳሳቢ ከመሆኑ የተነሳ በፓርቲዎች ስምምነት ፣በጣሊያን ሲልቪዮ ቤርሎስኮኒን ፣ እንዲሁም በግሪክ ጆርጅ ፓፓንድርዩን የተኩት የምጣኔ  - ሀብት ባለሙያ የሆኑ ነገር ግን በቀጥታ በህዝብ ያልተመረጡ ፣ ነገር ግን በአውሮፓ ህብረት ውስጥ የሰሩና በምጣኔ - ሀብት ጉዳዮች ላይ እውቀትና ልምድ ባላቸው ጠቅላይ ሚኒስትሮች ተተክተዋል ። ጉዳዩ በጣም አሳሳቢና መፍትሄን የሚሻ ከመሆኑ የተነሳ የፖለቲካ ስርአቱም ጭምር ለባለሙያዎቹ ስልጣኑን የለቀቀበት ሁኔታ እስከመፈጠር ደርሷል ።
 


ሌላው ደግሞ የአሁኗን አለማችንን የሚገልፀው ጉዳይ የበርካታ ሀገራት ህዝቦች ውስጣዊ ነፃነታቸውን ለመቀዳጀት ፣ ሙሉ የሆነ የዲሞክራሲያዊ መብታቸውን ከመጎናፀፍ እያደረጉ ያሉት ትግል ሲሆን ፣ የውጪ ጠላትን ከመቋቋም ባልተናነሰ ከውስጥ የሚነሱ አምባገነኖችን መታገልም አንዱና ዋነኛው የዘመናችን ዋነኛው የትግል መስክ ነው ። እ.ኤ.አ በ2012 ዓ.ም. በተለይ በአረብ አገራት ከታየው ህዝባዊ እንቅስቃሴዎች መረዳት እንደሚቻለው ጦርነት የሚካሄደው ከውጪ ወራሪዎች ጋር ብቻ አይደለም ። ለዘመናት በህዝቡ ላይ ተቀምጠው የቆዩ አምባገነኖችንም ለመጣል ጦርነቶችን ሊካሄዱ እንደሚችሉ ፣ በሰሜን አፍሪካ በሊቢያ በጋዳፊ ፣ በየመን ፣ በሶርያ የታዩት ስኬታማ እንቅስቃሴዎች አመላካች ናቸው ።    



ሌላው በአለም አቀፍ ደረጃ በአለማችን ሀገራት ላይ ያለው ፣ የሀገራት እርስ በእርስ ትስስር መጨመር ሲሆን ፤ ይህም በሉላዊነት ዘመን በግልፅ የሚታይ ጉዳይ ሲሆን ፣ «ሁላችንም በአንድ ጀልባ ላይ ነው የተሳፈርነው» የሚል አባባል አለ ። ይህም በአለማችን ላይ በአንዱ አካባቢ የሚፈጠር ችግር ወደ ሌላውም የአለም ክፍል በቀላሉ ሊስፋፉ እንደሚችል ለመረዳት የሚያስችል ሲሆን ፣ በአለም ላይ የምናያቸው ችግሮችም ሆኑ መልካም አጋጣሚዎች ወደ ተቀረው የአለም ክፍል በቀላሉ ይስፋፋሉ ፤ ለምሳሌም የሚሆነው የአለም የአየር ንብረት ለውጥ ለመላው አለም ችግር ሲሆን ፤ ሌሎችም ችግሮች  እንደዛው በፍጥነት ይሰራጫሉ ።    



እዚህም እዚያም በርካታ የአለም አቀፍ ምሳሌዎች የገቡበት ምክንያት ስለ ሀገራችን ለመረዳት አለምንም መረዳት ጠቃሚ መሰረት መሆኑን በማመን ሲሆን ፤ በአሁኑ ወቅት አገራዊ የሆኑ ችግሮች አንዳንዶቹ አለም አቀፋዊ ዳራ ያላቸው ናቸው ። ለምሳሌ የዋጋ ግሽበትን ብንወስድ መነሻው ከአገር ውስጥ ብቻ ሳይሆን ከአለም አቀፋዊ ካለው የዋጋ ጭማሬም ጭምር ነው ።



አለም አቀፋዊ ቴክኖሎጂዎችም ስላሉ አሁን የአለም ህዝብ ያለው ግንዛቤ ጨምሯል። በአለም ሀገራት መሀከል ያሉ ትስስሮች እየጨመሩ ስለሆነ አለም አቀፋዊ የሆነውን ተጨባጭ ሁኔታ መረዳት ለብዙ ምጣኔ - ሀብታዊም ሆነ ፖለቲካዊ እውነታዎችን ለመረዳት ያስችለናል ።



ለምሳሌ የአለም ምጣኔ - ሀብት ባደጉት ሀገራት መሀከል ብቻ ሳይሆን ፣ ብቅ ብቅና እየጎለመሱ ያሉ (Emerging) በመባል የሚታወቁት ሀገራትም ጭምር ያላቸው ትስርስር መጨመሩንና ፣ ከቀን ወደ ቀን በአለም ምጣኔ - ሀብት ላይ ያላቸው በጎም ይሁን አሉታዊ ተፅእኖ በመጨመር ላይ ይገኛል ። ለምሳሌ እ.ኤ.አ. በ2008 ዓ.ም. ተከስቶ በነበረው የአለም ምጣኔ - ሀብት ቀውስ ፣ የምእራብ ሀገራትን ካሉበት ቀውስ እንዲወጡ ያስቻላቸው የቻይናና እንዲሁም የሌሎች ብሪክስ በመባል የሚታወቁት ሀገራት ምጣኔ - ሀብት በእድገት ላይ ስለነበረ የተፈራው የምጣኔ - ሀብት ዝቅጠት (Depression) ቀርቶ ከአጭር ጊዜ የኢኮኖሚ መቀዛቀዝ (Recession) በኋላ እንደ ቀድሞው ባይሆንም ምጣኔ - ሀብታቸው ሊያገግም ችሏል ።



በተመሳሳይም በ2011 ተከስቶ በነበረው የአውሮፓውያን የእዳ ቀውስ ምክንያት አውሮፓውያን መጀመሪያ ላይ ቻይና ባላት ግዙፍ የውጭ ምንዛሪ ተቀማጭ ምክንያት ድጋፍ ልታደርግልናንና ገንዘብ ልታበድረን ትችላለች ብለው ቢጠብቁም ቻይና በማንገራገሯ ፣ እና አሜሪካም አቅሟ የደከመበት ጊዜ ስለነበረ ፣ የላቲን አሜሪካ ሀገራትም እንዲሁ ያን ያህል አቅም የሌላቸው በመሆኑ ፣ ወደ አፍሪካ አይናቸውን በማማተር አፍሪካ የአለምን ምጣኔ - ሀብት ከገባበት ቀውስ ላልታወጣ ትችላለች እስከማለት ደርሰዋል ፣ ቀድሞ በችግርና የምትታወቀው የአፍሪካ አህጉር ለዚህ መታሰቧ ራሱ የደረጃዋ መሻሻል ነው ሊባል ይችላል ፣ ይህም የአለም ምጣኔ - ሀብት ትስስር ደሀ ይባሉ የነበሩትን ሀገራትንም ጭምር እያካተተና ሀገራት ተፅእኖንና ተደማጭነት እያገኙ እንደሚሄዱ መገመት ይቻላል ።      



አሁን ባለው የአለማችን ሁኔታ ግን የየትኛውም ሀገር መሪ የሆነ ሰው ቢያንስ የምጣኔ - ሀብት መሰረታዊ ሀሳቦችን በሚገባ እሚረዳ መሆን አለበት ። የብዙ በተለይም ያደጉ ሀገራት ችግሮች በሀገር ውስጥ የምጣኔ ሀብትን እድገት ማስቀጠል፣ ስራ አጥነትን ፣ የዋጋ ግሽበትን መግታት ፣ የመሳሰሉት ፈተናዎች ናቸው ። ቀድሞ በነበረው አለም ግን የቅኝ ግዛትን መያዝ ፣ ግዛትን ማስፋፋት የመሳሰሉት ከጦርነት ጋር የተያያዙ ፈተናዎች የነበሩ ሲሆን ፤ የአሁኑን አለማችንን ለመረዳት መሰረታዊ የሆኑትን  የምጣኔ - ሀብት መርሆዎች መረዳት ጠቃሚ  ሲሆን የምጣኔ - ሀብት ምንነትን መረዳት ከማንኛውም ጊዜ በበለጠ አስፈላጊነቱ እየጨመረ የመጣበት ጊዜ ነው ።

ነገር ግን ይህ ብቻ ሳይሆን ዋናውም ማህበረሰብ የምጣኔ - ሀብትን ህግጋቱንና አካሄዱን መረዳት ዝንባሌ ቢኖረው ጥሩ ሲሆን ባደጉት ሀገራት ሳይቀር ያለው ማህበረሰብ ትኩረቱ በጎላ ብለው በሚታዩ ዋና ዋና የፖለቲካና የምጣኔ - ሀብት ጉዳዮች ላይ ነው እንጂ በምጣኔ - ሀብታዊ ጉዳዮች ላይ አይደለም ። ጥቂቶች የተማሩ ሰዎችና መሪዎች ብቻ የሚያውቁት ጉዳይ ብቻ ሳይሆን ሌላውም ማህበረሰብ ሊረዳው የሚችል ጉዳይ ነው ። እንደሚታሰበውም በጣም ረቂቅ ሙያዊ (Technical) አይደለም ።

ብዙሀኑ ህብረተሰብ የምጣኔ-ሐብት አሰራሮችን መረድዳት ቢችል የሰፋ የህሀቦ  ብት ልዩነት እንዳይኖር ፣ ንብረት በጥቂቶች እጅ ገብቶ ብዙሀኑ የጥቂቶች አገልጋይ ብቻ ሆኖ እንዳይቀር እና ፍትሐዊ የሆነ ህብረተሰብ እንዲፈጠር ያግዛል ።

No comments:

Post a Comment