Friday, February 6, 2015

ድና ዘንድሮ



የድሮዎቹ አባቶቻችን ድንበርን በማስከበር ፣ ጦርነት ወራሪን በመከላከል በመሳሰለው  የአርበኝነት ጀብድና ገድል ዘመናቸውን ሲያሳልፉ ባአንፃሩ ግን የአሁኑ ትውልድ ግን ሀብትን በማከማቸት ፣ ገንዘብን በመሰብሰብ ሲጠመድ ማየትና መስማት የተለመደ ነው ፡፡ ይህም የዘመኑ ትውልድና የቀድሞው ትውልድ ምን ያህል የተራራቀ የአስተሳሰብ አድማስ እንደነበራቸው የሚያሳይ ነው ፡፡ የዘመኑ ትውልድ ቁጥርና ስታትስቲክስ ላይ ሲያተኩር የቀድሞው ትውልድ ፖለቲካና ህግ ላይ ትኩረትን ያደርጋል ፡፡ የአሁኑ ትውልድ ገንዘብና ገንዘብ ነክ ጉዳዮች ላይ የበለጠ እውቀት ሲኖረው የቀድሞው ትውልድ ስለ ገንዘብም ሆነ ስለ ምጣኔ ሀብት የነበረው እውቀት ከአሁኑ ጋር የሚወዳደር አይደለም ፡፡ የቀድሞው ትውልድ ለአገሩ ቀናኢ በመሆን የአካልና የህይወት መስዋእትነትን በመክፈል አገሩንና ዳር ድንበሩን አስከብሮ አለፈ እንጂ በአብዛኛው በዚያ ሀብት የተጠቀመ እና በድሎት ተንደላቆ የኖረ አይደለም ፡፡ በአንፃሩ የአሁኑ ትውልድ በድህነት መማረሩ ለገንዘብ ከፍተኛ ፍቅር እንዲያድርበት ዋነኛ ምክንያት ሳይሆን አይቀርም ፡፡ ወደ ውጪ አገር በህጋዊም ሆነ ህጋዊ ባልሆነ መንገድ እሚሰደደው በአብዛኛው ወጣት በኢኮኖሚ ምክንያት ሲሆን በሚችለውም ይህንን ነባራዊ ሁኔታ ለመለወጥ በትግል ላይ ይገኛል ፡፡
የሀገራችን የፍትሀ ብሄር ዋናውን ህግና የወንጀል ዋናዎቹን ህግጋቶቹን ከነ ስነ-ስርአት ህጋቸው ጋር አብረው የወጡት በቀዳማዊ ሀይለስላሴ ጊዜ ሲሆን እስካሁን ድረስ የሚሰራበት የፍትሀ ብሄር ህጉ አሁንም ድረስ የዛሬ ስልሳ አመት በእርሳቸው ዘመነ መንግስት አክሊሉ ሀብተወልድ ጠቅላይ ሚኒስትር ሆነው በዘመኑ ፓርላማ የፀደቀው በነጋሪት ጋዜጣ የታተመው አዋጅ ነው ፡፡
      በእነኚህ ህግጋቶች መግቢያ ላይ ቀዳማዊ ሀይለስላሤ ያደረጓቸው ንግግሮች ይህንን ያመለክታሉ ፡፡ አስገራሚው ነገር በቀዳማዊ ሀይለ ስላሴ ዘመን የወጣውን የፍትሀ ብሄር ሆነ የወንጀል ህግ ኢህአዴግም ሆነ ደርግ ሲጠቀሙበት መቆየታቸው ነው ፡፡ በኋላ ላይ የመጡት መንግስታት ሀይለስላሴን በብዙ መንገድ የሚነቅፉ ቢሆንም ይሁንታቸውን በሰጡትና በእርሳቸው ዘመን በወጣው ህግ አገር ሲያስተዳድሩና ፍርድ ቤቶችም ውሳኔ ሲሰጡ ኖረዋል ፡፡ ደርግም ቢሆን በእርሳቸው ዘመን በወጣው ህግ ሲጠቀም ነው የቆየው የፍትሀ ብሄሩን ህግንም ሆነ የስነ ስርአት ህጉን ባያሻሽለውም ቆየት ብሎ ግን የጊዜያዊ ወታደራዊ አስተዳደር ደርግ በ1974 ዓ.ም. የተሻሻለው ልዩ የወንጀለኛ መቅጫ ህግ በአዋጅ ቁጥር 214 / 1974 በሚል አውጥቷል ፡፡ ደርግ መጀመሪያ ባወጣቸው አዋጆችም በፍርድ ቤት ሲደረጉ የነበሩ ክርክሮች በነበረው የፍትሀ ብሄርና የወንጀል ህግ እንደሚቀጥሉም አውጇል ፡፡ በኢህአዴግ ዘመን የወንጀል ዋናውን ህግ ብቻ (ስነ - ስርአት ህጉን ሳይጨምር) በ1997 ዓ.ም. ተሻሽሏል ፡፡
ዶ/ር አበራ ጀምበሬ የህግ ታሪክን በሚያወሳውና በሻማ አሳታሚ ድርጅት በታተመው ‹‹ የኢትዮጲያ የፍትህና የአፈፃፀም ስርአት ታሪክ ከ1426 - 1966›› በሚል ርእስ በታተመው መፅሃፋቸው ላይ በፃፉት መፅሀፍን ለቀዳማዊ ሀይስላሴ መታቢያ ሲያደርጉ ‹‹የኢትዮጲያ የዘመናዊ ህግ አባት›› ላሏቸው ለቀዳማዊ ሀይለስላሴ መታሰቢያ አድርገውታል ፡፡
ምንም እንኳ የሃይለ ስላሴ መንግስት በህግ በኩል ቀጥሎ ወደ ስልጣን ከመጡት መንግስታት የተሻለ ቢሆንም ነገር ግን የሰበር ስርአት የሚል ስያሜ የተሰጠው በዚያን ወቅት የዙፋን ችሎት በሚል ይታይ ስለነበረና የዙፋን ችሎት ምን አይነት እንደሆነና ፍርድ አጣሪ ወይንም የዙፋን ችሎት በሚል ስነ - ስርአት ህጉ ላይ የተቀመጠ ሲሆን ይህ ግን በአሁኑ ዘመን ጠቅላይ ፍርድ ቤት በሚገኘው የሰበር ሰሚ ችሎት የተተካ በመሆኑ አንዱ የፍትሀ ብሄር የስነ - ስርአት ህጉን ማሻሻል ከሚስፈልግባቸው ምክንያቶች እንዱ ይሄው ነው ፡፡
በ1958 ዓ.ም በወጣው የፍት ብሄር የስነ ስርአት ህግ መሰረት በቁጥር 359 መሰረት ፍርድ እንዲጣራ ስለሚቀርብ አቤቱታ ሲደነግግ የመጨረሻው ፍርድ ከተሰጠ በኋላ ለግርማዊ ንጉሰ ነገስት ዙፋን ችሎት አቤቱታ የሚቀርበው የመጨረሻው ፍርድ ከተሰጠ በኋላ ፍርዱ እንዲጣራለት በአንድ ወር ውስጥ መጠየቅ ይችላል ይላል ፡፡ በንጉስ ስርአት አንዱ እነ መንግስቱ ንዋይ መንግስት ንጉሰ ነገስቱን ለመገልበጥ የተነሱበት ምንክያት ሲገልጡ የህዝቡ ፍትህ ማጣትና ፍትህን ፍለጋ የንጉሰ ነገስቱን ደጅ ሲጠና መቆየቱን እና ይህም ያሳዝናቸው እንደነበረ ገልፀዋል ፡፡ ይሁን እንጂ የሰበር ሰሚ ስርአት መኖሩ አንድ አስፈላጊ እርምጃ ሲሆን ቀድሞ በንጉሰ ነገስቱ ዘመን ይህ ስርአት የግርማዊ ንጉሰ ነገስት የዙፋን ችሎት በሚል የሚታወቀው ሳይሆን አይቀርም ፡፡
በዚያው ስርአት የመጨረሻ ውሳኔን ሳያገኙ እስከ ሃያ አምስት አመታት ድረስ የቆዩ ጉዳዮች እንደነበሩ ይነገራል ፡፡ የዙፋን ችሎት የአሁኑን በአዋጅ የተቋቋመውን የሰበር ስርአት የሚረካ የነበረ ሲሆን ነገር ግን በአብዛኛው የሚመራው በራሳቸው በንጉሰ ነገስቱ በመሆኑ ግን ለህዝቡ የነበረው ተደራሽነት ግን ውሱን ነበረ ፡፡ የንጉሰን ደጅ ጠንቶ ንጉሱን ገብቶ እንዲያነጋግር የተፈቀደለትና ፣ ንጉሰ ነገስቱ ወደ አንዱ ጠቅላይ ግዛት ጉብኝትን ሲያደርጉ በአካል አግኝቶ ባነጋገረ ሰውና ከተፈቀደለት ፍትህ ይሰጠኝ ብሎ ጮሆ የንጉሱን ጆሮ ሊያገኝ ይችላል ፡፡
ነገር ግን ይህ በራሱ በፍትህ ስርአቱ ተቋማዊ መሰረት የሌለውና በንጉሱ ላይ ብቻ ተንጠልጥሎ የነበረው የመጨረሻ ፍርድን የማጣራት ስራ የግርማዊ ንጉሰ ነገስት ዙፋን ችሎት የሚል ስያሜ ነበረው ፡፡ በወቅቱ መሬትን፣ ርስትንና ቤትን የመሳሰለውን ብዙ አመታን ይፈጅ የነበረውን ክርክርን መፍትሄ ሊሰጥ ባለመቻሉ የፍትህ በተደራሽነት እንዲኮሰምን ማድረጉ የኋላ ኋላ በንጉሱ ስርአት ላይ ከተነሱት ቅሬታዎችና መማረር ዋነኛው ሊሆን በቅቷል ፡፡
ግሎሪያ ስቴይኔም የተባለ ደራሲ እንዳለው ‹‹ህግና ፍትህ ሁልግዜ አንድ ናቸው ማለት አይደለም ፡፡ አንድ በማይሆኑበት ጊዜ ህጉን ማፍረስ ለለውጥ የመጀመሪያው እርምጃ ሊሆን ይችላል››፡፡ በዚህም ለከሸፈው 1953 መፈንቅለ መንግስትና ለ1966 ህዝባዊ አብዮትና ለመንግስት ለውጥ ሰበብ የህበዝቡ ፍትህ ማጣት ዋነኛ ምክንያቶት ሆኖ ቀርቧል ፡፡ በሃገራችን ብቻም ሳይሆን በአውሮፓም ሆነ በተለያዩ የዓለማችን ክፍሎች ለአብዮቶችና ለለውጥ ዋነኛ ምክንያት የፍትህ በአግባቡ አለመስፈን መሆኑ የታሪክ አዋቂዎች የሚስማሙበት ጉዳይ ነው ፡፡ ብዙ ሃገራት መልካም የሆኑ ህግጋት ያላቸው ሲሆን ፣ የዓለም ዐቀፍ የሰብአዊ መብት ድንጋጌዎችን በህገ መንግስታቸው ያካተቱና በምክር ቤቶቻቸው ያፀደቁና ቤፋ የፈረሙና የተቀበሉ ናቸው ወደ ተግባር በመለወጥ በኩል ግን ዳተኝነት ይስተዋልባቸዋል ፡፡ በአሁኑ ወቅት በዓለም ላይ የምናየው የሰብአዊ መብት ጥሰት ቀድሞ የሰውን ልጅ ሰብአዊ መብትን ያከብራሉ ፣ የነፃነት ተምሳሌት ናቸው ይባሉ የነበሩ መንግስታትም ጭምር ስማቸው ሰብአዊ መብትን ባለማክበር ፣ ባለስልጣኖቻቸው በተደጋጋሚ በጦር ወንጀለኝነት ሲከሰሱ በመገናኛ ብዙሃን መስማት የተለመደ ነው ፡፡    
ሁሉን አቀፍ የህግ መፅሀፍ በሚል ርእስ በአቶ አንዳርጌ ሹምዬ በ2006 በተፃፈ መፅሀፍ ላይ በመግቢያው ላይ እንዲሁ ‹‹በሀይለ ስላሴ ስርአት ዘመን ዳኞች ሆነው ሲሰሩ የነበሩት ባለሞያዎች ህጎችን አንብቦ ከመረዳትና ከመተርጎም ጀምሮ በማስረጃ ምዘናና የውሳኔ አፃፃፍ አሁን ካለው የዳኝነት ስርአት የተሻሉ ነበሩ ፡፡ የሚገርመው ነገር ከቤተክርስትያን ትምህርት የዘለለ ሌላ ህግ ትምህርት ቤት ገብተው የተማሩ አለመሆናቸው ነው››  
የቀድሞው ንጉሰ ነገስት ቀዳማዊ ሀይለስላሴ የፍትሀ ብሄር ህግን ሲያውጁ በነጋሪት ጋዜጣው ላይ መግቢያው ላይ ባደረጉት ንግግር ላይ እንዲህ ብለዋል፤
 ‹‹ማናቸውም ህግ የሰዎችን መብትና ግዴታ ለመግለፅ እንዲሁም በመካከላቸው ያሉት ግንኙነቶች የሚተዳሩበትን መሰረታውያን ሃሳቦች ለመግለፅ የወጣ ሲሆን ህጉ ከወጣላቸው ሰዎች ልብ የሚደርስ ፍላጎታቸውን ፣ልምዳቸውን ወይም የተፈጥሮ ፍትህን የሚጠብቅ ካልሆነ በቀር ዋጋ ሊኖረው አይችልም ››
‹‹እኛ ያቋቋምነው የፍትሀ ነገስት ኮሚሲዮን ይህን የፍትሀ ብሄር ህግ ሲያዘጋጅ በተከበረውና በጥንቱ በጥንቱ ፍትሀ ነገስት መፅሀፍና ፍርድ በመዝገብ መፃፍ ከተጀመረ ወዲህ የተገለፁትን ጥንታዊ የሆኑትን የንጉሰ ነገስት መንግስታችንን ታላቅ የህግ ልምዶችና አቋሞችን በመመልከትና በተለይም ለንጉሰ ነገስት መንግስታችንና ለተወደደው ህዝባችን የሚያስፈልጉትን በማሰብ ነው››
‹‹ማናቸውም ሰው ለኑሮው አስፈላጊ የሆኑትን መብቶቹንና ግዴታዎቹን ሁሉ ያለ ችግር እንዲገባው ለማድረግ አቅደንና በዚህ ህግ ውስፅጥ የሚገኙትን ቃላቶች ግልፅ ሆነው እንዲዘጋጁ አድርገናል ››
‹‹የፍርድ ምንጭ የጥበብና የሀብት ማግኛ በሆነ ሁሉን በሚችል በእግዝአብሄር አሰሪነት ይህ ህግ ላሁኑ ህዝባችንና ለመጪው ትውልድ ለሰላሙና ለደህንነቱ እንደሚሆን እናምናለን››[1]
      ይህም የሚያሳየው የቀድሞዎቹ አባቶቻን ለህግ ይሰጡ የነበረውን የበለጠ ትኩረትን ያሳያል ፡፡ ራሳቸው ቀዳማዊ ሀይስላሴ ከአንድ የእንግሊዝ ዩንቨርስቲ በህግ የክብር ዲግሪ ማግኘታቸው የሚታወቅ ሲሆን እንደነ አክሊሉ ሀብተወልድን የመሳሰሉ ከፍተኛ ባለስልጣኖቻቸውም ከአውሮፓ ታላላቅ ዩንቨርስቲዎች በህግ የተመረቁ ነበሩ፡፡ ለረጅም ዘመናት የንጉሰ ነገስቱ ጠቅላይ ሚኒስትር የነበሩት አክሊሉ ሀብተወልድ ከፈረንሳይ ከሚገኘው የሰርቦን ዩንቨርስቲ በህግ የተመረቁ ነበሩ ፡፡
‹‹ይህን የፍትሀ ብሄር ህግን በማርቀቅ ደረጃ በንጉስ ሃይለስላሴ ግዛት ዘመን የፍርድ ሚኒስትር የነበሩት ክቡር ንርአዮ ኢሳያስ ሲሆኑ ለዚህ ዝግጅት የፕሮፌሰር ግራቨን ረቂቅና እ.ኤ.አ. በ1908 ዓ.ም. የወጣውን የህንድ የፍትሀ ብሄር ስነ ስርአት ህግ በምንጭነት የተገለገሉ መሆኑን ህገ ታሪክ ያስረዳናል››[2] ፡፡ ከዚህም እምንረዳው ይህ የህንድ ህግ በዘመናዊ የህግ አስተዳደር ሰፊ ልምድ ከነበራትና በወቅቱ የህንድ ቅን ገዢ ከነበረችዋ ከእንግሊዝ ተወስዶ  እንደተዘጋጀና በወቅቱ ህንድ የእንግሊዝ ቅኝ ግዛት ስለነበረች በእንግሊዝ ህግ በመመስረት እንደተዘጋጀ መገመት ይቻላል፡፡ የሀገራችንን የፍትሀ ብሄር ህጉንም ሆነ የስነ - ስርአት ህጉን ያነበበ ሰው ከእንግሊዝ ህግ ጋር ያለውን ተመሳስሎ መረዳት ይችላል ፡፡ 


[1] የኢትዮጲያ ንጉሰ ነገስት የፍትሀ ብሄር ህግ ፣ 1952 ዓ.ም. ነጋት ጋዜጣ  ቁጥር 1 በተለይ የወጣ፣ አዲስ አበባ
[2] አንዳርጌ ካሴ ሹምዬ ሁሉን አቀፍ የህግ መፅሀፍ ፣ መጋቢት 2006 ዓ.ም. አ.አ.

No comments:

Post a Comment